የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንና የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት በዛሬው ዕለት ተፈራርመዋል (1/3/2015)።

endc civil societies

በስምምነቱ መሰረት ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ጋር ጠንካራ ግንኙነት በመፍጠር የምክክር ሂደቱን ለማገዝ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የሚኖራቸውን አዎንታዊ ሚና የሚያጎላ ነው ተብሎ ይታመናል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ በትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነዱ ፊርማቸውን ባኖሩበት ወቅት “የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ስራው ውስብስብ ቢሆንም ዛሬ ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ጋር ያደረግነው ጥምረት ሁሉንም አካታች በሆነ መልኩ ስራችንን ለመከወን ድጋፍ የሚሰጠን ሲሆን የሀገራዊ ምክክር ሂደቱን ስኬታማ ለማድረግ ይረዳናል” ብለዋል።
የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤትን ወክለው የስምምነት ሰነዱ ላይ ፊርማቸውን ያኖሩት የምክር ቤቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሄኖክ መለሰ በበኩላቸው “እውነተኛ ማኅበረሰባዊ ሽግግርና አንጻራዊ ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ የሚቻለው ሕዝብን በማዳመጥና ሕዝብ ያለውን ሀብትና እሴት ከግንዛቤ ያስገቡ የችግር መፍቻ አካሄዶችን በመቀየስ ሲሆን ሃገራዊ ምክክሩም ስኬታማ እንዲሆን በተቻለው ሁሉ ለደገፍ ይገባዋል” ብለዋል።