የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን

ስለ ኮሚሽኑ

ርዕይ

 

እጅግ መሠረታዊ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሀገራዊ መግባባት ተፈጥሮ ማየት፡፡

 

ተልዕኮ


በኢትዮጵያ መሰረታዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ለተፈጠሩ ልዩነቶችና አለመግባባቶች ወሳኝ ምክንያቶችን በጥናትና በሕዝባዊ ውይይቶች በመሰብሰብ ፣ በተለዩ አጀንዳዎች ላይ ሀገራዊ ምክሮችን በማካሄድ፣ ምክረ ሀሳቦችን በማቅረብ እና ለተግባራዊነቱም የመከታተያ ስርዓ በመዘርጋት ለሀገራዊ መግባባት ምቹ ሁኔታ መፍጠር፡፡

የኢትዮጵያ የሀገራዊ ምክክር መርሆዎች

 

  • አካታችነት፤
  • ግልፅነት፤
  • ተዓማኒነት፤
  • መቻቻል እና መከባበር፤
  • ምክንያታዊነት፤
  • የምክረ ሃሳቦች ተግባራዊነት እና አውደ ተኮርነት፤
  • ገለልተኛ አመቻችነት፤
  • የአጀንዳዎች ጥልቀት እና አግባብነት፤
  • ዲሞክራሲ እና የሕግ የበላይነት፤
  • ብሔራዊ ጥቅም፤
  • ሀገራዊ ባህላዊ እውቀቶችንና እሴቶችን መጠቀም።

የኮሚሽኑ ዓላማ

 

  • በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል መሠረታዊ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ለተጠሩ ልዩነቶች ወሳኝ ምክንያቶችን በመለት እና ውይይቶቹ የሚካሄዱባቸውን ርዕሰ ጉዳዮች በመለየት ምክክር እንዲደረግባቸው ማመቻቸት፤
  • የሚካሄዱት ሀገራዊ ምክክሮች አካታች፣ ብቃት ባለውና ገለልተኛ በሆነ አካል የሚመሩ፣ የአለመግባባት መንስዔዎችን በትክክል በሚዳስስ አጀንዳ የሚያተኩሩ፣ ግልፅ በሆነ የአሠራር ሥርዓት የሚመሩ እና የምክክሮቹን ውጤቶች ለማስፈፀም የሚያስችል ዕቅድ ያላቸው እንዲሆኑ በማድረግ ውጤታማ የሆኑ ሀገራዊ የምክክር ሂደት ተግባራዊ ማድረግ፤
  • የሚካሄዱት ሀገራዊ ምክክሮች በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል እንዲሁም በመንግሥት እና በሕዝብ መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻል፣ መተማመን የሰፈነበትና አዲስ የፖለቲካ ሥርዓት ለመፍጠር በሚያስችል አግባብ ውይይቶቹ እንዲካሄዱ ሥርዓት መዘርጋት፤
  • ከምክክሮቹ የተገኙ የመፍትሔ ምክረ ሃሳቦች በሥራ ላይ እንዲውሉ ድጋፍ በማድረግ በዜጎች መካከል እንዲሁም በመንግሥትና በሕዝብ መካከል መተማመን የሰፈነበት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት በሀገር አቀፍ ደረጃ እንዲገነባ ማስቻል፤
  • ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ ውስጣዊ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት የሚያስችል የፖለቲካ ባህል ለማዳበር እና ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ምቹ መደላድል መፍጠር፤
  • ወቅታዊ ችግሮች ዘላቂ በሆነ መንገድ ተፈተው አስተማማኝ ሰላም የሚረጋገጥበትን የፖለቲካ እና የማኅበራዊ መደላድል ማመቻቸት፤
  • ለአገራዊ መግባባት እና ጠንካራ ቅቡልነት ያለው ሀገረ መንግሥት ለመገንባት ጽኑ መሠረት መጣል ናቸው።

የኮሚሽኑ ተግባርና ኃላፊነቶች

 

  • ምክክሮችን የሚያመቻቹና ሚያስፈጽሙ፣ የተለያዩ ጥናቶችን የሚያካሂዱ እና ምክረ ሃሳቦችን የሚያመነጩ ኮሚቴዎችን እና የባለሙያ ቡድኖችን ያቋቁማል፤
  • ከዚህ በፊት በመንግሥታዊም ሆነ መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት የተደረጉ ሀገራዊ የምክክር ሂደቶችን እና የተገኙ ውጤቶችን ያጠናል፣ በቀጣይ ለሚያካሂዳቸው ሀገራዊ ውይይቶች በግብዓትነት ይጠቀማል፤
  • በተለያዩ የፖለቲካ እና የሃሳብ መሪዎች እንዲሁም የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል ሀገራዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ያሉትን ልዩነቶች በጥናት፣ በሕዝባዊ ውይይቶች ወይም ሌሎች አግባብነት ያላቸውን መንገዶች በመጠቀም ይለያል፤
  • በዚህ አንቀጽ ንዑስ አቀጽ (፫) መሰረት በተገለፁት ዘዴዎች የለያቸውን ጉዳዮች መሰረት በማድረግ የምክክር አጀንዳዎችን ይቀርፃል፣ ምክክር እንዲደረግባቸው ያመቻቻል፣ ምክክሮችን እና ውይይቶችን ያሳልጣል፤
  • ከመላ ሀገሪቱ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን እና አካላትን የሚወክል ተሳታፉዎች የሚሳተፍባቸው፣ ሀገራዊ መግባባት ለማምጣት የሚያስችሉ የተለያዩ የምክክር ስብሰባዎችን በፌደራል እና በክልሎች ደረጃ እንዲካሄዱ ያመቻቻል፤
  • በሀገራዊ የምክክር ጉባዔ ላይ የሚሳተፉ ተሳታፉዎችን ግልፅ በሆኑ መሥፈርቶች እና የአሠራር ሥርዓት መሠረት ይለያል፣ በምክክሮች ላይ እንዲሳተፉ ያደርጋል፤ ይህን የተመለከተ ዝርዝር መመሪያ ያወጣል፤
  • ምክክሮቹ በኮሚሽነሮች ወይም የኮሚሸነሮች ምክር ቤት በሚሰይማቸው አወያዮች አማካኝነት እንዲመሩ ያደርጋል፤ በአወያይነት የሚመድባቸዉ ሰዎችም በተቻለ መጠን በዚህ ሕግ አንቀጽ ፲፫ ላይ የተመለከቱትን ለኮሚሽነርነት የሚያበቁ መስፈርቶችን የሚያሟሉ መሆናቸዉን ያረጋግጣል፤
  • በምክክር ሂደቶች የሚደረጉ ምክክሮችን ቃለ ጉባዔ የሚዙ፣ የቀረቡ ምክረ ሃሳቦችን የሚያጠናቅሩ እና አደራጅተው ለኮሚሽነሮች ምክር ቤት የሚያቀርቡ ባለሙያዎችን ይመድባል፤
  • የጽህፈት ቤቱን የውስጥ የአሠራር ሥርዓት፣ የምክክር አጀንዳዎች ወይም አርዕስት የሚመረጡበትን የሚመለከት፣ በሀገራዊ ውይይቶች ላይ የሚሳተፉ አካላት የሚለዩበትን ሥርዓት ለመዘጋትና መሰል ተግባራትን ለማከናወን የሚያስችሉ ውስጠ ደንቦችን እና መመሪያዎችን ያወጣል፣ በሥራ ላይ ያውላል፤
  • የሀገራዊ ምክክር ጉባዔ አጀንዳዎችን፣ የምክክሮቹን ሂደት፣ በምክክሮቹ የተገኙ ምክረ ሃሳቦችን እንዲሁም ምክረ ሃሳቦቹ በተግባር ላይ ሊውሉ የሚችሉበትን ሥልት የሚገልጽ ሰነድ በማዘጋጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ለአስፈጻሚ አካሉ እና ሌሎች የሚመለከታቸዉ የመንግስት አካላት ያቀርባል፤ ለሕዝብም ይፋ ያደርጋል፤
  • መንግሥት ከሀገራዊ ውይይቶች የሚገኙ ምክረ ሃሳቦችን በተግባር ላይ ለማዋል እንዲችል ግልፅ እና ተጨባጭ የሆነ ዕቅድ እንዲዘጋጅ አስፈላጊውን እገዛ ያደርጋል፤
  • የምክረ ሃሳቦቹን አፈፃፀም መከታተል የሚያስችል ሥርዓት ይዘረጋል፤ ዓላማውን ለማስፈፀም የሚያስፈልጉ ሌሎች ተግባራትን ያከናውናል።

የኮሚሽኑ ምክር ቤት ተግባር እና ሥልጣን

 

  • የሕዝብ ምክክር የሚደረግባቸውን አጀንዳዎች በዝርዝር በመፈተሽ ምክክር እንዲደረግባቸው መወሰን፤
  • በኮሚቴዎች ተዘጋጅተው የሚቀርቡ እና በሕዝባዊ ውይይቶች የተገኙ ምክረ ሃሳቦችን በዝርዝር በመፈተሸ እና በማጠናቀር ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለአስፈፃሚ አካላትና ሌሎች የሚመለከታቸዉ የመንግሥት አካላት እንዲቀርብ ማፅደቅ፤
  • የጽህፈት ቤቱን ዓመታዊ በጀትና ዕቅድ መርምሮ የማፅደቅ፤
  • የጽህፈት ቤቱን አጠቃላይ ሪፖርት መርምሮ የማፅደቅ፤
  • አስፈላጊ ኮሚቴዎችን የማቋቋም፤
  • በክልሎች የጽህፈት ቤቱን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች እንዲቋቋሙ የመወሰን፤
  • የጽህፈት ቤቱን የኦዲት ግኝት መርምሮ የማፅደቅ፤
  • የምክር ቤቱ ዋና ኮሚሽነርና ምክትል ዋና ኮሚሽነር በተመሳሳይ ጊዜ በሥራ ገበታቸው ላይ ለተከታታይ አስር ቀናት ካልተገኙ ከአባላቶቹ መካከል ጊዜያዊ ሰብሳቢ የመምረጥ፤
  • የጽህፈት ቤቱን መዋቅራዊ አደረጃጀት የማፅደቅ፤
  • የጽህፈት ቤቱን ኃላፊ ሹመት የማፅደቅ፤
  • አዋጁን ለማስፈፀም የሚያስፈልጉ መመሪያዎችን የማውጣት፤
  • የኮሚሽነሮች የሥነ ምግባር መመሪያ የማውጣት፤
  • የጽህፈት ቤቱን የመተዳደሪያ ደንብ የማውጣት፤
picture 1